6. ፌዘኛ ጥበብን ይሻል፤ ሆኖም አያገኛትም፤ዕውቀት ግን ለአስተዋዮች በቀላሉ ትገኛለች።
7. ከተላላ ሰው ራቅ፤ከከንፈሮቹ ዕውቀት አታገኝምና።
8. የአስተዋዮች ጥበብ መንገዳቸውን ልብ ማለት ነው፤የተላሎች ሞኝነት ግን መታለል ነው።
9. ተላሎች በሚያቀርቡት የበደል ካሳ ያፌዛሉ፤በቅኖች መካከል ግን በጎ ፈቃድ ትገኛለች።
10. እያንዳንዱ ልብ የራሱን መራራ ሐዘን ያውቃል፤ደስታውንም ማንም ሊጋራው አይችልም።
11. የክፉዎች ቤት ይፈርሳል፤የቅኖች ድንኳን ግን ይስፋፋል።
12. ለሰው ቀና መስሎ የሚታይ መንገድ አለ፤በመጨረሻ ግን ወደ ሞት ያደርሳል።
13. በሣቅ ጊዜ እንኳ ልብ ይተክዛል፤ደስታም በሐዘን ሊፈጸም ይችላል።
14. ልባቸውን ከጽድቅ የሚመልሱ የእጃቸውን ሙሉ ዋጋ ይቀበላሉ፤ደግ ሰውም ወሮታውን ያገኛል።
15. ተላላ ሰው ሁሉን ያምናል፤አስተዋይ ግን ርምጃውን ያስተውላል።
16. ጠቢብ ሰው ጥንቁቅ ነው፤ ከክፉም ይርቃል፤ተላላ ግን ችኵልና ደንታ ቢስ ነው።
17. ግልፍተኛ ሰው የቂል ተግባር ይፈጽማል፤መሠሪም ሰው አይወደድም።
18. ብስለት የሌላቸው ተላላነትን ይወርሳሉ፤አስተዋዮች ግን ዕውቀትን እንደ ዘውድ ይጭናሉ።
19. ክፉዎች በደጎች ፊት፣ኀጥኣንም በጻድቃን ደጅ ያጐነብሳሉ።
20. ድኾችን ወዳጆቻቸው እንኳ ይጠሏቸዋል፤ባለጠጎች ግን ብዙ ወዳጆች አሏቸው።
21. ጎረቤቱን የሚንቅ ኀጢአት ይሠራል፤ለተቸገሩት የሚራራ ግን ቡሩክ ነው።
22. ክፉ ነገር የሚያቅዱ ከትክክለኛው መንገድ ይወጡ የለምን?በጎ ነገር የሚያቅዱ ግን ፍቅርንና ታማኝነትን ያተርፋሉ።
23. ለፍተው የሠሩት ሁሉ ትርፍ ያስገኛል፤ከንቱ ወሬ ግን ወደ ድኽነት ያመራል።
24. ጠቢባን ብልጥግና ዘውዳቸው ነው፤የተላሎች ተላላነት ግን ፍሬው ከንቱነት ነው።